የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲፓርቲ መሠረታዊሰነድ
መሠረታዊ ሰነድ
የባልደራስ ፓርቲን ከአገር አቀፍ መሆን ምክንያት በማድረግ ይህ የባልደራስ መሠታረዊ ሰነድ ፓርቲው ሲመሰረት ባፀደቀው መርሃ ግብር /ፕሮግራም/ እና ለመጭው የፓርቲው ሃገር አቀፍ ጉባኤ ተሻሽሎ በሚቀርበው ፕሮግራም ላይ በመመስረት የፓርቲውን መርሆዎች፣ ራዕይ ፣ተልዕኮ፣ እሴቶች እና ዋና ዋና ተግባራትን አጠር እና ሰብሰብ አድርጎ በማመልከት፣ ባልደራስን ለመቀላቀል ለሚፈልጉ ወገኖች ፓርቲው የቆመለትን ዓላማ እንዲገነዘቡ በማሰብ የተዘጋጀ አጭር ሰነድ ነው፡፡
ይህ ሰነድ በባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ዙሪያ ለተሰበሰብንና ለመሰባሰብ ለምንፈልግ ወገኖች፣ ከሕይወት ተሞክሯችን እና ከእውቀታችን ተነስተን፣ አገራችንን እና ሕዝቧን በሚመለከቱ መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ያሉንን እምነቶች፣ አመለካከቶችን እና ግንዛቤዎችን የሚያንፀባርቁ ናቸው፡፡
በዚህም መሰረት፡-
መርሆ፡- ስንል በዚህ ሰነድ በራዕይ ላይ ያመለከትናትን እና ሆና ማየት የምንፈልጋት ኢትዮጵያ ምን እንደምትመስል የቀረፀልን ማለታችን ነው፡፡
ተልዕኮ ስንል ደግሞ መርሆዎቻችንን መሠረት በማድግ በራዕያችን የሳልናት ኢትዮጵያ እውን እንድትሆን ለማድረግ ማከናወን ያለብንን ተግባራት ለመወጣት ማንገብ የሚገባንን እሴቶች የሚያመለክት ነው፡፡
መሠረታዊ መርሆዎች
የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ መሠረታዊ መርሆዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡
- ኢትዮጵያ የጥንታዊ አኩሪ ሥልጣኔ ባለቤት እና የብዙ ሺህ ዘመናት የሃገረ- መንግሥትነት ታሪክ ያላት በመሆኗ ፓርቲያችን ይኮራል፡፡
- በኢትዮጵያ ሉኣላዊነትና አንድነት መከበር በጽናት ያምናል፡፡
- ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅም መከበር እና ደህንነት ቅድሚያ ይሰጣል፡፡
- ኢትዮጵያ በብዝሀ- ሕዝብ የተዋበች፣ የተቀላቀለ እና የተወራረሰ ማኅበረሰብ ያለባት የአንድ ሕዝብ አገር ናት ብሎ ፓርቲያችን ያምናል፡፡
* ባልደራስ አገር አቀፍ ፓርቲ ከሆነበት ከነሐሴ 23/2016 ዓ.ም ጀምሮ የድርጅታዊ መዋቅሩን በመላ ኢትዮጵያ የመዘርጋት ጥረቱን ጀምሯል፡፡ በኢትዮጵያ ሕዝብ እንድነት እና በታሪካዊት ኢትዮጵያ ሉዓላዊነት የማይናወጥ እምነት ያላችሁ ኢትዪጵያዊያን ሁሉ ባልደራስን እንድትቀላቀሉ ፓርቲያችን በአጽንኦት ጥሪውን ያቀርባል፡፡
- ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ባሰፈኑ አገሮች የሚገኙ ማህበረሰቦች የተለያዩ ባህሎቻቸውን/ቋንቋን ጨምሮ/ አስከብረውና አበልፅገው ለመያዝ የሚያስችላቸውን መብት በሁለቱም ዓይነት መንግሥት አወቃቀር ማለትም በአሃዳዊም ሆነ በፌደራላዊ ስርዓት ብዝሃነትን በማስከበር ረገድ ልዩነት እንደሌለ ለመገንዘብ ይቻላል፡፡ በሁለቱም የመንግሥት አወቃቀር ቅርፆች ቢሆን ሥልጣንን ለአካቢዎች በማከፋፈል እና ብዘሃነትን በማስተናገድ ረገድ ልዩነት እንደሌላቸው ከአሃዳዊነት አወቃቀር እንግሊዝን እና ስፔንን ከፌድራላዊ አወቃቀር ደግሞ አሜሪካንን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ፌድራላዊ የመንግሥት አወቃቀር ተከትለ የፖለቲካ ፓርቲዎች በነገድ/ብሔረሰብ ስም እንዳይጠሩ በሕገ መንግስት የከለከለች አፍሪካዊት አገር ናይጀርያም በምሳሌነት ልትጠቀስ ትችላለች፡፡ ናይጀሪያ ዘመናትን የፈጀ የእርስ በርስ ጦርነት አሰልፋ የፖለቲካ መረጋጋት በማስገኘት፣ በዚህም ላይ ተመስርታ በኢኮኖሚ እድገቷ ደቡብ አፍሪካን በልጣ ከአፍሪካ የአንደኛነት ደረጃ ልትጎናፀፍ የቻለችው ከ200 በላይ ከሆኑት ነገዶቿ መካከል ትላልቆቹ የሃውሳ-ፉላኔ፣ ዮሩባ እና የኢቦ ብሔረሰቦች የፖለቲካ ኤሊቶቸ በዚህ የፖለቲካ ፎርሙላ ላይ ሙሉ ስምምነት ላይ በመድረሳቸው መሆኑን ፓርቲያችን ባልደራስ ይገነዘባል፡፡ የስምምነቱ ዝርዝር የሚከተለው ነው፡፡ ለሃገራዊ ሥልጣን ለመወዳደር የተቋቋመ ወይም የሚቋቋም የፖለቲካ ፓርቲ አባልነት የመኖሪያ አካባቢ/ክልል፣ የብሔረሰብ ማንነት፣ የተወሳነ ቋንቋ ተናጋሪነት፣ የሃይማኖት ገደብ ሳይኖርበት ለሁሉም የናይጀሪያ ዜጎች ክፍት መሆኑ ህገ መንግሥታዊ ግዴታ ነው፡፡ በናይጀሪያ የተቋቋሙ የፖለቲካ ፓርቲዎች ስምም ሆነ አርማ ወይም ገዥ መፈክር ከነገድ/ብሔረሰብ ወይም ክልል ጋር የተያያዘ መሆን የለበትም፤ ወይም የፓርቲው እንቅስቃሴ ከሃገሪቱ የተወሰነ ማህበረሰብ ጥቅም ጋር የተሳሰረ እንደሆነ ማድረግም ሆነ ማስመሰል አይችልም፡፡ በናይጀሪያ የፋይናንስ እና የኢኮኖሚ ተቋማት የብሔረሰብ ስም መያዝ በሕግ የተከለከለ ነው፡፡
በሃገራችን በኢትዮጵያ የመንግሥት አወቃቀር ጥያቄ ፌደራላዊ ይሁን አሃዳዊ የሚለው ጥያቄ ከሌሎች ከሚሻሻሉ የሕገ መንግሥት አንቀጾች ጋር ማለትም ከሃገራዊ የሥራ ቋንቋ፣ እና የፌደል አመራረጥ፣ ሃገራችን የፕሬዚዳንታዊ ወይስ ፓርላሜንታዊ የፖለቲካ ስርዓት ተከተል፣ የኢትዮጵያ የምርጫ ስርዓት የአብላጫ ድመፅ ይሁን ወይስ የተመጣጣኝ ድምጽ አስጣጥ ስርዓት እና የፌድራል አድያማት የወሰን አከላለል መመዘኛዎች ወዘተ…ጋር ተዳብሎ ለህዝብ ሪፈረንደም ቀርቦ መወሰን አለበት፡፡ ለሃገራዊ ስልጣን የሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በህገ መንግሥት አስገዳጅነት ንፍቀ ክበባዊ (ዮኒቨርሳል) የሆነ ፖለቲካዊ አመለካከቶችን (ማለትም ሊብራል፣ ሶሻል ዲሞክራቲክ፣ ሶሻሊስት ወዘተ… እንጅ የብሔረሰብን ማንነት ወደ ፖለቲካ ደረጃ የሚያሳድግ ፖለቲካ ማራመድ የለባቸውም ብሎ ባልደራስ ያምናል፡፡
- የአዲስ አበባ ጉዳይ የኦህዴድ/ብልፅግና መንግሥት ከሕገ መንግሥቱ ውጭ በጉልበቱ ተጠቅሞ የኦሮሚያ ዋና ከተማ እንድትሆን እያደረገ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ባልደራስ በህዝብ ተመርጦ ስልጣን ቢይዝ አዲስ አበባ የኢትዮጵያ እና የሁሉም ኢትዮጵያውያን ዋና ከተማ ሆና እንዳኖረች በዚሁ መልክ እንድትቀጥል፤ ይኸም ነጥብ በአዲሱ ወደፊት በሚዘጋጀው ህገ መንግሥት ቦታ እንዲሰጠው ያደርጋል፡፡ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት አዲስ አበባ ራሷን የቻለች አስተዳደራዊ ግዛት የነበራት ሲሆን የቆዳ ስፋቷም122,000 ካሬ ኪሎ ሜትር ነበር፡፡ በህወሓት/ኢህአዴትግ የመጀመሪያ የስልጣን ዘመን በሽግግሩ ወቅት ጊዜ አዲስ አበባ ክልል 14 በሚል ስያሜ ተከልላ ነበር፡፡ ባልደራስ ወደፊት የህዝብ ምርጫ አሸንፎ ስልጣን ቢይዝ አዲስ አበባ ራሷን የቻለች የፌድራል አድያም /ራስ ገዝ አስተዳደር/ ሆና፣ ቀጥታ ተጠሪነቷም ለአዲስ አበባ ህዝብ እንጅ ለፌድራል መንግሥት እንዳይሆን ይዳርጋል፡፡
- ተፈጥሮአዊ የሆነውን የማንነት ጉዳይ የባህላዊ እሴቶችን በማክበር እና ሁሉም ባህሎች በእኩልነት ደረጃ እንዲከበሩ ወይም የባህል ብዝሃነት የሚያበረታታ፣ይሁንና ባህላዊ ማንነት ከመንግሥትታዊ/ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ነጥሎ ለማዋቀር የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት እንሚያስፈልግ እና እንደሚቻል ፓርቲያችን ያምናል፡፡
- ኢትዮጵያ የብዙ ባህሎች ባለቤት በመሆኗ ለመልካም ባህሎቿ እንክብካቤ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡
- ታሪክና ባህልን ካነሳን አይቀር፣ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርሶች እንዲከበሩ እና በብልጭልጭ ግንባታ ሽፋን እንዳይፈርሱ፣ቅርሶች ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው እንዲያዙ ፓርቲያችን በአክብሮት ያሳስባል፡፡
- ማንኛውም የኢትዮጵያ ዜጋ በዘውግ፣ በእምነት፣ በጾታ ሳይበላለጥ በሕግ ፊት እኩል የመሆን መብትና ግዴታ አለው፡፡
- በኢትዮጵያ መንግሥት እና ኃይማኖት ሙሉ በሙሉ መነጣጠል አለባቸው ብሎ ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡ ገዢው ፓርቲ “መደመር” የሚለውን አስተሳሰብ ከብልፅግና ወንጌል ጋር በማስተሳሰር የብልፅግና ፓርቲ የሚባል ኃይማኖትን ከመንግሥት ሥልጣን ጋር የቀላቀለ/ “Theocraclic”/ ኃይማኖታዊ መንግሥት ማቋቋሙ የመንግስትና የኃይማኖት መነጣጠልን መሠረታዊ የዲሞክራሲ መርህ ይፃረራል ብለን እናምናለን፡፡ ከዚህም ፖለቲካ እና እምነትን ካቀላቀለ አካሄድ በመነሳት የኦህዴድ/ብልፅግና/መንግሥት በኢትዮያ ነበባር የኦርቶዶክስና የሱኒ እስልምና እምነቶች ላይ የሚያደርሰውን ጥቃት ፓርቲያችን ባልደራስ በፅናት ይቃወማል፡፡
- ኢትዮጵያዊ ዜጋ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ እና በማኅበራዊ ጉዳዮች እኩል የመሳተፍ እድል /Equal Opportunity/ እና በየትኛውም የአገሪቱ ማዕዘን ተንቀሳቅሶ የመኖር፣ የመሥራት እና ሃብት የማፍራት መብቱ የማይገሰስ ሊሆን ይገባል፡፡
- የማስመሰል ሳይሆን እውነተኛ ዲሞክራሲ ለአገራችን ህልውና እና ለፖለቲካችን መዘመን እንዲሁም መረጋጋት መሠረት መሆኑን ይገነዘባል፡፡
- ፖለቲካችን በዜግነት /በግለሰብ/ መብት ላይ የተዋቀረ መሆን ይገባዋል፡፡
- የግለሰብ መብት ሙሉ በሙሉ እስከተከበረ ድረስ የቡድን መብት የማይከበርበት ሁኔታ እንዳማይኖር ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡
- የአገር ውስጥ የአስተዳደር ወሰኖች በቋንቋ ላይ ሳይሆን በጂኦግራፊያዊ መመዘኛዎች፣ለኢኮኖሚ ልማት ባላቸው አመችነት፣ በአስተዳደራዊ ቅልጥፍ እና የሕዝብ አሰፋፈር መሠረት ያደረጉ መመዘኛዎች ላይ ሊመሠረቱ ይገባል ብሎ ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡ የሃገራችን የውስጥ የአስተዳደር ወሰኖች በነዚህ መመዘኛዎች መመሥረታቸው ከብሔረሰብ ተኮር ፖለቲካ ይልቅ ተዘንግቶ የቆየው ሃገራዊ ፖለቲካ ቅድሚያ እንዲሰጠው ያደርጋል ብለን እናምናለን፡፡
- ሃገራችን ኢትዮጵያ ከፓርላሜንታዊ ስርዓት ይልቅ ፕሬዚዳንታዊ ስርዓት መከተሏ፣ በአብዝሃ ህዝብ ምርጫ ፕሬዚዳንቱ/ቷ መመረጡ/ጧ፣ ጠባብ የሆነው የነገድ ፖለቲካ በተፋጠነ ሁኔታ እየተዳከመ እንዲሄድ እንደሚያደርገው ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡
- የሃገራችን የምርጫ ስርዓት ቀድሞ 50+1 ካገኘነው (First past the post/ ይልቅ የተመጣጠኝ /Proportional/ ምርጫ ስርት አንዲሆን ፓቲያችን ይጥራል፡፡
- በአሁኑ ወቅት ከማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ ለተከሰቱ ችግሮች ከወታደራዊ መፍትሄ ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሄ መስጠቱ ለአገራችን ፖለቲካ መረጋጋት ቁልፍ ተግባር መሆኑን ያምናል፡፡ የሃገራችን ፖለቲካ ሳይረጋጋ ስለ ኢትዮጵያ ልማት መመኜት እና በፖለቲካ የታሸ “የእድገት” አሃዝ ማነብነብ ከከንቱ ፕሮፖጋንዳነት እንደማይዘል ፓርቲያችን ይገነዘባል፡፡
- የመንግሥት ሥልጣን በሥልጣን ክፍፍል መርህ ላይ የተገነባ እና ያልተማከለ የፖለቲካ ስልጣን እንዲሆን ተደርጎ መዋቀር ይኖርበታል፡፡
- ለህዝብ የቀረበ የፖለቲካ ስልጣን መዘርጋት፤ የፖለቲካ ተጠያቂነት እና የግልጸኝነት ባህልን ማጠናከር ፣መልካም አስተዳደርን ማስፈን ለሁንተናዊ እድገት መተኪያ የሌለው ሚና የሚጫወት መሆኑን ያምናል፡፡
- የዜጎችን ሰብአዊ መብት ማክበር እና የአገራችንን ፖለቲካ ማዘመን የማይነጣጠሉ መሆናቸውን ከበለፀጉ አገሮች ልምድ እና ተመክሮ መገንዘብ ይቻላል፡፡
- በኅብረተሰባችን ውስጥ በትምህርት ስርዓቱ ውስጥ ይሰጥ የነበረውን ዜጎችን በጥሩ የግብረገብነት መሠረት ላይ ተኮትኩተው እንዲያድጉ ረድቶ የነበረውን ማኅበራዊ እሴት እንደገና እንዲገነባ ለማድረግ የግብረገብነት ትምህርት በስርዓት ትምህርት ውስጥ እንዲካተት መደረጉ አስፈላጊ እና ጠቃሚ መሆኑን ያምናል፡፡
- ፓርቲያችን ባልደራስ አማርኛ የአገሪቱ ብሔራዊ ቋንቋ እንዲሁም የፌድራል መንግሥቱ የሥራ ቋንቋ ሊሆኑ እንደሚገባ ያምናል፡፡ በቋንቋ ላይ ሳይሆን በቁጥር 14 ላይ በተጠቀሱ መመዘኛዎች የሚመሠረቱ የፌድራል አድያማት የራሳቸውን ቋንቋ የመምረጥ መብታቸው እንደተጠበቀ ሁኖ፣ አማርኛ እና እንግሊዘኛን በመደበኛ ትምህርትነት በስርዓተ ትምህርታቸው ሊያካትቱ እንደሚገባ ፓርቲያችን ባልደራስ ይገነዘባል፡፡
- በሃገራችን የስርዓተ ትምህርት ውስጥ አማርኛ እና እንግሊዝኛ ከ3ኛ ክፍል በላይ ከየአካባቢው ቋንቋ ጋር በመደበኛ ትምህርትነት እንዲያገለግሉ እንዲደረግ መደረጉ ሃገራዊ/ኢትዮጵያዊ ማንነትን ለማጎልበት አስፈላጊ መሆኑን ያምናል፡፡
- ሃገራችን ኢትዮጵያን ከሌሎች አገሮች ልዩ የሚያደርጋት ሃገር በቀል የግዕዝ ፊደሏ ስለሆነ ይኸ አኩሪ ቅርስ ሃገራዊ መገልገያ እንዲሆን በአዲሱ ህገ መንግሥትም ቦታ እንዲሰጠው ፓርቲያችን ይጥራል፡፡
- የአገራችን የኢኮኖሚ አስተዳደር በገበያ ኢኮኖሚ መርሆች እና በግል ይዞታ ላይ የሚመሰረት ሆኖ፣ የመንግሥት ኢኮኖሚያዊ ጣልቃገብነት ገደብ ተበጅቶለት በአመዛኙ በሃገራዊ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የፖሊሲ አመራር ሰጭነት እና ክትትል ተግባራት ላይ ያተኮረ ሊሆን ይገባል ብለን እናምናለን፡፡
- በአቅም ማነስ ምክንያት የግሉ ዘርፍ ሊገባበት በማይችል የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ እና የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ ላይ የመንግሥት ተሳትፎ መኖሩ አማራጭ የሌለው የኢኮኖሚ ልማት ፖሊሲ አካል ሊሆን እንደሚገባ ፓርቲያችን ይረዳል፡፡
- ፓርቲያችን ባልደራስ የገብያ ኢኮኖሚ እንጅ “ነፃ ገብያ” የሚባል ክስተት ኑሮ እንደማያውቅ እና አሁንም እንደሌለ ይገነዘባል፡፡ የሀገራችን የኢኮኖሚ ልማት ሞዴል ከኒዮ-ሊበራል ሃይሎች ጥገኝነት እና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋሞች ተፅዕኖ ነፃ በሆነ መልኩ እንዲካሄድ ለማድረግ የሀገራችን የኢኮኖሚ ልማት ሞዴል የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት (Democratic Developmental State Economic Model) የኢኮኖሚ ልማት ሞዴልን የተከተለ ሊሆን እንደሚገባው ፓርቲያችን ያምናል፡፡ ሀገራችን ይህን አይነት የኢኮኖሚ ልማት ሞዴል ስትከተል ብቻ ነው ኢኮኖሚዋን ተከታታይነት ባለው ሁኔታ ልታሳድግ እና በማኅበራዊ ክፍፍል ሂደት ፍትሃዊነትን ለማስፈን የምትችለው፡፡ ይህም ጥቂት ሃብታሞች ተፈጥረው አብዛኛው የሀገሪቱ ሕዝብ ያጣ የነጣ ድሃ እንዳይሆን፣ ድህነትን እና የድሃውን የህብረተሰብ ክፍል ቁጥር በቁርጠኝነት እና በየጊዜው በመቀነስ የመካከለኛ መደቡን ቁጥር በማስፋፋት ላይ ያተኮረ የኢኮኖሚ ልማት ሞዴል መከተል ማለት ነው፡፡ይህ ዓይነት የኢኮኖሚ ልማት ሞዴል የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ለውጥ በማስገኘት፣ የዘመነ እና ተከታታይነት ያለው የኢኮኖሚ እድገት እና ልማትን እውን ለማድረግ ይቻላል ብሎ ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡
- የኦህዴድ/ብልፅግና መንግሥት እመራበታለሁ የሚለውን “ሃገር- በቀል የኢኮኖሚ ተሃድሶ መርሃ ግብር” የሚለውን የ10 ዓመት የኢኮኖሚ መርሃግብር “ሃገር በቀል” የሚል ስያሜ ቢሰጠውም፣ በአይ.ኤም.ኤፍ አመራር እና እገዛ የተነደፈ፣ አይ፣ኤም.ኤፍ እና ዓለም ባንክ በታደጊ አገሮች ላይ የሚጭኑትን “የመዋቅር ማስተካከያ ፕሮግራም” (Structural adjustment Programe) ሙሉ ለሙሉ የተቀበለ፣ የሃገራችን ኢኮኖሚ የማክሮ ኢኮኖሚ ቀውስ ያራጋጋል በሚል ሽፋን የሃገራችን ኢኮኖሚ ከእዳ ጫና አዙሪት እንዳይወጣ የሚያደርግ ፖሊሲ ስለሆነ፣ ባልደራስ ይህን የገዥው ፓርቲ እየተከተለ ያለው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ለሃገራችን ኢኮኖሚ መረጋጋት ያመጣል፣ የኢኮኖሚ እድገትም ያስገኛል የሚል እምነት የለውም፡፡ ይህን የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ታደጊ አገሮች የኢኮኖሚ አስተዳደር ውስጥ ጣልቃ እየገቡ/Micro manage/ የኢኮኖሚ ፖሊሲ አመራር ሰጭ የሆኑበትን አካሄድ ፓርቲያችን ባልደራስ አጥብቆ ያወግዛል፡፡
- የኦህዴድ/ ብልፅግና መንግሥት እየተከተለ ያለው የኢኮኖሚ ፓሊሲ ግብርናን በማዘመን ከግብርና ጋር የተያያዙ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎችን እንዲሁም የማዕድን ዘርፍን በማሳደግ ላይ ያተኮረ ሳይሆን የአገልግሎት ዘርፍ አካል የሆኑትን የከተሞችን ማስዋብን፣ ለቱሪዝምና ለቴክኒዎሎጅ ልማት ልዩ ትኩረት የሰጠ ነው፡፡ ለዚህም የቤተ መንግሥት የጫካ ፕሮጀክትን፣ የኮሪደር ልማትን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡ እነዚህ ለእይታ የሚያብለጨልጩ ፕሮጀክቶች የሰፊውን ህዝብ የኑሮ ሁኔታ በመለወጥ እና ደረጃውን በማሻሻል ረገድ የሚያበረክቱ አስተዋጽኦ በእጅጉ ኢምንት ነው፡፡ ይህ ዓይነት የልማት ትኩረት ሃገራችን በስፋት ባላት እምቅ ሃብት መሬትና የሰው ጉልበት ላይ ተመሥርቶ ተከታታይነት ያለው ፈጣን እድገት በማስመዝገብ መዋቅራዊ ለውጥ በማስገኘት ረገድ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ አነስተኛ ነው፡፡ ስለሆነም ፓርቲያችን ባልደራስ የሃገሪቱ ዋንኛ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ትኩረት በአሁኑ ጊዜ የኦህዴድ- ብልፅግና መንግሥት እየተከተለ ባለው የተሳሳተ የኢኮኖሚ ልማት ሞዴልና ፖሊሲ ምክንያት በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን የኢኮኖሚ እና የኑሮ ሁኔታ ድቀት ከግምት ውስጥ አስገብቶ፣ ይህን አስከፊ ሁኔታ በተፋጠነ ሁኔታ ለመቀየር የሚያስችል መሆን አለበት ብሎ ፓርቲያችን ባልደራስ ያምናል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ ህዝብ የኑሮ ሁኔታ በሁሉም የኑሮ መሻሻል መለኪያዎች ማለትም በሰብዓዊ ልማት አመልካቾች (Human Development Index)፣ በፈርጀ ብዙ የድህነት አመልካቾች (Multi Demensicnal Poverty Index) ዜጎች በኑሯቸው ላይ ያላቸው የእርካታ ደረጃ (Percoption of Wellbeibening) ቢታይ በጣም አስከፊ እና አሳፋሪ ሁኔታ ላይ የሚገኝ መሆኑን ፓርቲያችን ባልደራስ ይገነዘባል፡፡ በመሆኑም ባልደራስ ምርጫ አሸንፎ ሥልጣን ቢይዝ፣ በዋነኝነት የሚከተለው የኦኮኖሚ ፖሊሲ የሃገራችን ኋላቀር ኢኮኖሚ በተፋጠነ ተከታታይነት ባለው ሁኔታ እድገት እንዲያስመዘግብ በማድረግ መዋቅራዊ ለውጥ በማስገኘት ረገድ ሊረዳ የሚችል መሆኑን የሚያረጋግጥ ይሆናል፡፡
- ኋላቀር በሆነ የኢኮኖሚ አወቃቀር ምክንያት አገራችን አሳሳቢ ለሆነ የተፈጥሮ ሃብት ብክነት እና ለበርሃማነት መስፋፋት ተጋልጣ ያለችበትን ሁኔታ በመለወጥ፣ ለደን እና እጽዋት ሃብት መበራከት ለመላ የተፈጥሮ ሃብቷ (የእንስሳት ሃብቷን ጨምሮ) እንክብካቤ እና ልማት ልዩ ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ ፓርቲያችን ባልደራስ ይገነዘባል፤በመሆኑም ሁኔታውን ለመለወጥ በተፈጥሮ ሃብት እንክብካቤ ረገድ መትጋት እንደሚያስፈልግ ያምናል፡፡
- ፓርቲያችን ባልደራስ መሬት የኦኮኖሚ መገልገያ መሳሪያ እንጅ የፖለቲካ መሰሪያ መሆን የለበትም ብሎ ያምናል፡፡ መሬት የሃገር ዜግነት መብት መገለጫ እንጅ የብሔረሰብ ይዞታ ሊሆን አይገባም፡፡ መሬትን በግል የመያዝ የመሸጥ የመለወጥ መብት ለሁሉም ዜጎች መሰጠት ያለበት፣ የማይገሰስ የዜጎች መብት መሆን አለበት ብሎ ባልደራስ ያምናል፡፡ ለዚህም መብት ሕገ መንግስታዊ መሆን ይታገላል፡፡ ይህ ፖሊሲ ግን የሃገራችንን የአርብቶ አደር አካባቢ መሬትን በወል የመያዝ መብት ቀጣይነት አይመለከተም፡፡
ራዕይ
ሃገራችን ኢትዮጵያ የአንድ ወጥ ሃገር – መንግሥት ግንባታን በመጀመር ረገድ ታሪክ ከመዘገባቸው ታላላቅ ሥለጣኔ ካበባቸው አገራት ከቆዳሚዎቹ ሃገሮች እንዷ ብትሆንም፣ በየጊዜው በተከሰቱ አደናቃፊ ምክንያቶች የተነሳ የሃገረ- መንግሥት ግንባታን ከዘመናዊነት ጋር አጣምራ ለመጨረስ ሳትችል ቀጥታ፣ እነሆ በቅድመ አያቶቻችን ከባድ ተጋድሎ የተገነባው አገር በአሁኑ ጊዜ የሃገሪቱን ታሪክ የተጠየፈ ስርዓት በተጠናወተው የእርስ በእርስ ጦርነት አባዜ ምንያት ለመፍረስ አደጋ ተጋልጣለች፡፡
በተለይ ከ1983 ወዲህ ባሉት ዓመታት የሃገረ መንግሥት ሥልጣን በነገድ ፖለቲካ በታወሩ ጥቅመኛ የጉልበተኛ ቡድኖች ተጠልፎ፣ በነገድ ማንነት ዙሪያ የተከለለ አግላይነት እንደመንግሥታዊ አስተዳደር ስልት ተይዞ፣ አሁን ያለንበት የውድቀት አዘቅት ላይ ተደርሷል፡፡ በ1985፣ በ1997፣ በ2010 ስርዓታዊ ለውጥ ለማምጣት ሶስት እድሎች ቢከሰቱም፣ አርቆ የማሰብ ክፍተቶች አይለው እና ደንድነው እድሎቹ መና ሁነው ቀርተዋል፡፡
በመሆኑም ይችን ታሪካዊ አገር ከመፍረስ ለማዳን ስርዓታዊ ለውጥ ያስፈልጋታል፡፡ ስርዓታዊ ለውጥ ሲባል ጠባብ የሆነው የነገድ ብሔርተኝነት ተለውጦ የሃገሪቱን ዜጎች ሉዓላዊነት የሚያከብሩ ዘላቂ ዲሞክራሲያዊ አውታሮች ሊዘረጉ እና ዘመናዊ የፖለቲካ ተላቶቿ የሚፈሩዋት ባህል በተለይ 70% በሆነው የሃገሪቱ ወጣት ትውልድ ውስጥ እንዲሰርፅ ሊደረግ ይገባል፡፡
የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ራዕይ፣ በማይገሰስ የሃገር ሉዓላዊነት እና የአንድ አገር የዜግነት መብት ማዕቀፍ ስር የእያንዳንዱ ዜጋ ፖለቲካዊ፣ ሰብአዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ መብቶች የተከበሩባት፣እኩልነት የሰፈነባት፣ በውስጧ ያሉ ልዩ ልዩ የዘውግ ማኅረሰቦች ባህሎች፣ ቋንቋዎች እና እምነቶች የተከበሩባት፣ ሰላሟና መረጋጋቷ የተረጋገጠባት፣ በዳበረ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ላይ የተገነባ ሁለንተናዊ እድገትና ብልጽግና የተላበሰች፣ ዜጎቿ የሚኮሩባት ጠላቶች የሚፈሩዋት ገናና እና ታላቅ አገር ሆና ማየት ነው፡፡
ተልዕኮ
የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ተልዕኮ፣ባልደራስ በብዙሃኑ ሕዝብ ፍላጎትና ነፃ እና ፍትሃዊ ምርጫ ተመርጦ የመንግሥት ሥልጣን በመያዝ የፓርቲውን መርሆዎች መነሻ በማድረግ የፓርቲያችን የባልደራስ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ፖሊሲዎችን ተግባራዊ በማድረግ በፓርቲው ራዕይ ላይ የተበሰረችውን ዲሞክራሲያዊት እና ዘመናዊት ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ነው፡፡
የባልደራስ ለእውነተኛ ዲምክራሲ ፓርቲ ተግባራት
- ፓርቲያችን በአገራችን ለሚታዩ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ችግሮች ምንጭ የሆነው ሕገ መንግሥት እና በቋንቋ ላይ የተመሰረው መንግሥታዊ አወቃቀር በሕዝብ ተሳትፎ በሚገለፅ “ሪፈረንደም” እንዲቀየር ተግቶ ይሠራል፡፡
- በነፃ፣ በፍትሃዊ እና በሰላማዊ ምርጫ የሕዝብን አመኔታ በማግኘት የመንግሥት ሥልጣን ይዞ በዚህ ሰነድ ጠቅለል ባለ መልኩ የተጠቀሱ ፖሊሲዎች በየዘርፉ በሚዘጋጁ ዝርዝር ፖሊሲዎች ተግባራዊ ለማድረግ ይተጋል፡፡
- ፓርቲያችን የሚቀርፃቸው ፖሊሲዎች ሥልጣን በዲሞክራሲያዊና በዲሞክራሲያዊ መንገድ ብቻ እንዲያዝ የሚተልሙ ይሆናሉ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ህዝቦች ሳይሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ የአገሪቱ ሉአላዊነት መገለጫና ባለቤት የሆነበት አዲስ ህገ መንግሥት እንዲነደፍ አበክሮ ይሠራል፡፡
- በነፃ እና ፍትሃዊ ምርጫ ፓርቲያችን ለሥልጣን ባይበቃ የሰላማዊ የተቃዋሚ ፓርቲ ሚናውን በማጎልበት ሥልጣን የያዘው ፓርቲ የሚከተላቸው እና በተግባር የሚተረጉማቸው ፖሊሲዎች ለአገር እና ለህዝብ ጥቅም የሚሰጡ እንዲሆኑ ገንቢ አስተያዬቶችን ያቀርባል፡፡ ለሀገር የማይበጁ ተግባራት ሲፈፀሙ ባልደራስ ጠንክሮ ይሞግታል፡፡ የፖሊሲዎቹን ስህተተኛነት ለሕዝብ በመጠቆም በሕዝብ ሰላማዊ ግፊት እንዲስተካከሉ ለማድረግ በጽናት ይሠራል፡፡
- በሃገራችን የሚካሄድ ምርጫ በተመጣጣኝ ውክልና (Proportional Representation) ላይ የተመሰረተ የምርጫ ስርዓት እንዲሆን ይታገላል፡፡
- ከሕዝብ ልዕልና እና ከአገር አንድነት ውጭ የግልም ሆኑ የወል መብቶች ሊጠበቁ የሚችሉበት፣ በአገሪቱ የሚገኙ የተለያዩ ባህሎች የሚከበሩበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደማይችል በማመን፣ ፓርቲያችን የሚከተላቸው ፖሊሲዎች ለህዝብ አንድነት፣ ብልጽግና እና ልማት ቅድሚያ የሚሰጡ ሆነው እንዲቀረፁ ያደርጋል፡፡
- ባልደራስ ያለ ነፃና ገለልተኛ መንግሥታዊ ተቋማት ግንባት በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ሽግግር ሊሳካ ይችላል ብሎ አያምንም፡፡ በመሆኑም ፓርቲያችን ለነፃ እና ገለልተኛ ተቋማት መገንባት እና መጠናከር ልዩ ትኩረት ይሰጣል፡፡ ከዚህ አንፃር የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አወቃቀር እና የሕዝብና የቤት ቆጠራ ኮሚሽን፣ የሽግግር ፍትህ ኮሚሽን፣ የተመዘበረ የህዝብ/የመንግሥት ሃብት አጣሪና አስመላሽ ኮሚሽን፣ የሃገር ውስጥ ወሰን ጉዳዮች ኮሚሽን፣ የመሬት ይዞታ ኮሚሽን ወዘተ… ከማናቸውም ዓይነት የመንግሥት ተፅዕኖ ነፃ ሆነው የሚደራጁበት እና የሚሠሩበት ሁኔታ እንዲፈጠር ተግቶ ይሠራል፡፡ ገለልተኛ እና ነፃ የፍትሕ፣ የዳኝነትና የአቃቤ ሕግ ሥርዓት እንዲዘረጋ፣ ገለልገተኛነትና ከፍተኛ የሙያ ብቃትን የተላበሱ የመከላከያ፣ የደህንነት እና የፖሊሲ ኃይሎች እንዲገነቡ ለማድረግ በጽናት ይሠራል፡፡
- ፓርቲያችን የአገራችን ዲሞክራሲያዊ ሽግግር ያለነፃ ፕሬስና መገናኛ ብዙኃን እውን ሊሆን እንደማይችል አጥብቆ ያምናል፡፡ ከዚህም እምነቱ በመነሳት የአገራችን የመገናኛ ብዙኃን በገለልተኛነት አቋም እና በከፍተኛ የሙያ ብቃት ላይ ተመስርተው እንዲገነቡ እና እንዲሰሩ በማድግ ረገድ ተገቢውን የስልጠና ድጋፍ ማግኘታኘታቸውን ፣ ሥራቸውን በተገቢው የሙያ ስነምግባር መሠረት ማካሄዳቸውን ይከታተላል፡፡
- ፓርቲያችን ያለነፃ እና ገለልተኛ የሲቪክ እና የሕዝባዊ ማኅበራት ህልውና አገራችን ወደ ዲሞክራሲ ሥርዓት መሸጋገር እንደማትችል ያምናል፡፡ በዚህ መሰረት ነፃ የሲቪክ፣ የሙያ፣ የጾታ፣ የእድሜ፣ የሠራተኛ እና የገበሬ ማኅበራት እንዲቋቋሙና ጠንክረው እንዲሠሩ አበክሮ ይጥራል፡፡
- የአገር ውስጥ እና የውጭ የተራድኦ ድርጅቶች በነፃነት እንዲሠሩ ለአገሪቱ እድገት የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ ሊዳብር የሚችልበት በተገቢ የመንግስታዊ ክትትልና ቁጥጥር እንዲታገዙ ይደረጋል፡፡
- የአገራችንን ማኅበራዊ ልማት የሚያፋጥኑ ከአገራችን ተጨባጭ ሁኔታዎች ጋር የተጣጣሙ የትምርት እና የጤና ፖሊሲዎች ተቀርፀው የትምህርትና እና የጤና አገልግሎቶች እንዲስፋፉ ባልደራሥ አበክሮ ይሠራል ፡፡
- በአገራችን የትምህርት ሥርዓት ባለፉት ሰለሳ ዓመታታ ሲሠራበት የቆየው በሃሰተኛ የታሪክ ትርክት ላይ የተመሰረተው ሥርዓተ ትምህርት እንዲቀየር እና ወጣቱ ትውልድ እውነተኛውን የአገሩን ታሪክ ተምሮ ትክክለኛ ማንነቱን እንዲያውቅ ይደረጋል፡፡ ለዚህም ከአገሪቱ ታሪክ የሚመነጩ ጠቃሚ የአስተዳደር ዘይቤዎች እንዲቀስሙና ስርዓት ተበጅቶላቸው እንዲጎለብቱ ጠንክሮ ይሠራል፡፡ ትምህርት በሃሳብ ልዕልና የሚያምን ከዘውግ ማንነት የተላቀቀ አገራዊ የአመለካከት እና የውይይት ባህል ያዳበረ፣ አለመግባባቶችን በውይይትና በመቻቻል ለመፍታት የሚጥር የሰለጠና እና የዘመነ ዜጋ ለማፍራት የሚያስችል እንዲሆን ለማድረግ ባልደራስ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል፡፡
- የግለሰብ ሃብት ተገቢውን ህጋዊ ጥበቃ (Secure legal rlgths to Private Property) እንዲያገኝ የአገራችን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በፍትሃዊ አካሄድ ላይ በተመሰረተ የገበያ ውድድር አማካኝነት የሚመራ መሆኑ እንዲረጋገጥ ፓርቲያችን ተግቶ ይሰራል፡፡
- የኢኮኖሚ እና የማኅበራዊ እድገትን እንዲሁም ልቀትን (Excellence) የሚያፋጥኑ እና የሚያዳብሩ ፖሊሲዎችን ፓርቲያችን ይነድፋል፡፡ ልቀትን የሚያበረታቱ እና ዘመናዊነትን የሚያፋጥኑ ተቋማት እንዲገነቡ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ያምናል፡፡ የብቃት ማረጋገጫና የደረጃ መዳቢ ተቋማት ከማናቸውም ፖለቲካዊና የጥቅም ተፅእኖ ነፃ በሆነ ሁኔታ እንዲሰሩ አቅምና ብቃታቸውን እንዲዳብር ለማድረግ ይሰራል፡፡ ጥራት ላይ ያተኮረ የገበያ ውድድር እንዲስፋፋ ይጥራል፡፡ አገር በቀል እውቀትን ከዘመናዊ እውቀት ጋር የሚያዛምዱ ተግባራት ከፍተኛ ድጋፍ እንዲያገኙ ጥረት ያደርጋል፡፡
- ከፍተኛ እውቀትና የሥራ ልምድ ያዳባሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን በአሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በሌሎችም ውጭ ሃገሮች በርከት ባለ ቁጥር ይገኛሉ፡፡ የእነዚህ በትውልድ ኢትዮጵያዊ የሆኑ ግልሰቦች ጥሪታቸው ለሃገር ኢኮኖሚ የሚረዳ ከመሆኑ ባሻገር በተለይ እውቀታቸው እና የሥራ ልምዳቸው በገንዘብ የማይለካ በመሆኑ፣ የሃገራችንን ኢኮኖሚ በማሳደግ ረገድ የእስካሁኑ ተሳትፏቸው ውስን በመሆኑ፣ እነዚህ በእውቀት እና በሥራ ልመድ የዳበረ ተሞክሮ ያላቸው ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ፓርቲያችን ለፖለቲካ ሥልጣን ከመወዳደር መብት ውጭ የጥምር ዜግነት መብት እንዲያገኙ፣ ይህ ጉዳይ በሃገሪቱ ህገ መንግሥት ውስጥ እንዲካተት ጥረት ያደርጋል፡፡
የፓርቲያችን እሴቶች
የሚከተሉት የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ እሴቶች ናቸው፡፡
- ሐሰትን መጠየፍና ለእውነትና ለትክክለኛ አሠራር መቆም፣
- በሰብአዊ ግንኙነታችን ቀና እና ትሁት መሆን፣ አክብሮትን ማስቀደም፣
- በማኅበረሰባችን ውስጥ እንደነውር ከሚቆጠሩ ተግባራት እራስን ማራቅ፣
- ውሳኔዎችን ለማስተላለፍ የአርቆ አሳቢነትን እና የአስተዋይነትን ጠባይ ለመላበስ ያለሰለሰ ጥረት ማድረግ፣
- የሌሎች ሰዎች ሃሳቦችን ማክበር፣ የሃሳብ ልዩነትን በውይይት ለመፍታት ብርቱ ጥረት ማድረግ፣
- ከግብዝነት፤ ሁሉን አውቃለሁ ከሚል የጉረኛነት እና የጀብደኛነት ጠባይ መራቅ፣ ከቁጡ ግልፍተኛ ባህርያት እራስን መጠበቅ፣ ትንሽ ትልቅ ሳይሉ ማናቸውንም ግንኙነት በትህትና መንፈስ መምራት፣
- በዜጎች እኩልነት ማመን እና ለአንድነት መቆም፣ ይህን እምነትም በተግባር ማሳየት፣
- የመናገር፣ የመፃፍ፣ የመደራጀት መብትን በነፃነት ለመግለጽ ያለማወላወል መቆም፣
- ከአገር እና ከህዝብ ጥቅም በላይ የግል ጥቅምን አለማስቀደም፣
- የሚሠሩ ሥራዎችን ሁሉ በሃላፊነት ስሜት መሥራት፣ ተጠያቂነትን አለመፍራት፣
- ጎሣን፣ ነገድን/ ብሔረሰብን ሃይማኖትን፣ ዝምድናን፣ ጾታዊ ግንኙነትን መሠረት በማድረግ አድልኦ አለመፈፀም፣ ሙሰኝነትን በጽኑ መዋጋት፣በዚህ የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ
- ተቋማዊም (Structural / institutional Corruption) ሆነ አስተዳደራዊ (Administrative Corruption) እንዲሁም ግልሰባዊ (Individual Corruption) ሙሰኝነትን በፅናት ለመዋጋት የሚያስችል ስርዓት እንዲዘረጋ ያደርጋል፡፡
ደንብ
ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ጥር 4/2012 ዓ.ም በክልል አቀፍ ፓርቲነት ከተመዘገበበት ዕለት ጀምሮ የተቋቋመበትን የሕዝብ ጥያቄዎች አንግቦ ታግሏል፡፡ ባልደራስ የሰላማዊ ትግል መርህን በመከተል ለኢትዮጵያ ሕዝብ መብት እና ጥቅሞች መከበር እየታገለ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያን ሕዝብ በስፋት የሚያሳትፍ የፖለቲካ መስመር መዝርጋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ አስፈላጊውን ሕጋዊ ሂደት በማሟላት ነሀሴ 23/2016 ዓ.ም ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሀገር አቀፍ ፓርቲነት ምዝገባ እና እውቅና ሠርቲፊኬት ወስዶ እየታገለ ይገኛል፡፡
በዚሁ መሰረት ፓርቲያችን ባልደራስ በሀገር አቀፍ ደረጃ አባላትን የመመልመል እና የማደራጀት ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ የፓርቲውን የእስካሁን የአባላት መተዳደሪያ ደንብ ሰፋ ያለ ቢሆንም ፣የፓርቲው ደንብ ተጨምቆ በተለይ ለመጭው የፓርቲ ጉባኤ እየተዘጋጀ ካለው አዳዲስ አባላት ሊያውቁት ይገባል የምንላቸው የደንቡን አንኳር ነጥቦች ከዚህ በታች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡
አባልነት
አንቀፅ 1
መሥራች አባል
የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲን ለመመስረት የተመዘገቡና፣ በመስራች አባልነት ዝርዝራቸው ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተላለፉ እና በአዲሱ ፓርቲ ለመታቀፍ ስማቸዉ በዝርዝር የተገለፁ ሁሉ የፓርቲው መስራች አባላት ናቸው፡፡
7.2. እጩ አባል
- ዕድሜው 18 ዓመትና ከዚያም በላይ የሆነ፣ በፖለቲካ ለመሳተፍ በህግ ገደብ ያልተጣለበት፣ የፓርቲውን ዓላማዎችና እምነቶች የተቀበለና ለኢትዮጵያ ህዝብ የሥልጣን ባለቤትነትና ለተግባራዊነታቸውም ለመታገል ዝግጁ የሆነ
- የፓርቲውን ወርሃዊ መዋጮ ለመክፈልና ሌሎች ግዴታዎችን ለመወጣት ፈቃደኛ የሆነ
- በብሄረሰብ ፣ በቋንቋ፣ በኃይማኖት፣ በፆታ፣ በቀለም ወይም በማንኛውም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መመዘኛ በሰዎች መካከል ልዩነት የማያደርግ
- ለኢትዮጵያ እድገት የማያወላውል አቋም ያለው፣ የኢትዮጵያን ሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነትና የበላይነት የሚቀበልና በአገሪቱ እውነተኛ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲሰፍን ለመታገል የወሰነ፣ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የሆነ የፓርቲው አባል ለመሆን የፓርቲውን አባልነት ማመልከቻ ቅጽ ሲሞላ ይህን ተግባር እንዲያከናውን ኃላፊነት የተሰጠው አካል ተቀብሎ ጥያቄውን ያስተናግዳል
- አንቀፅ 7.2 ውስጥ ባሉት 4 ንዑስ ቁጥሮች ውስጥ የተዘረዘሩትን የሚያሟላ ግለሰብ የፓርቲው እጩ አባል ተብሎ እስከ ሦስት ወር ይቆያል
- እጩ አባል በፓርቲው የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የመሳተፍ መብት ቢኖረውም፣ የመምረጥና የመመረጥ እንዲሁም በፓርቲው ውሳኔዎች ላይ ድምጽ የመስጠት መብት አይኖረውም፡፡
7.3 ሙሉ አባል
በፓርቲው እጩ አባል ሆኖ ከተመዘገበበት ቀን ጀምሮ እስከ ሶስት ወር መጨረሻ ድረስ የእጩ አባልነት ግዴታውን በአግባቡ የተወጣ ዕጩ አባል የፓርቲው ሙሉ አባል ይሆናል፡፡ ከሶስት ወር በኋላ በሚመለከተው አካል መልስ ካልተሰጠው ሙሉ አባል እንደሆነ ይቆጠራል
በፓርቲው የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ተጠይቆ አባል ለመሆን ፈቃደኝነቱን የገለፀ ኢትዮጵያዊ ዜጋ፣ በስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ውሳኔ መሰረት በአንቀፅ 7.2 ተራ (ተ.ቁ 5) ላይ የተጠቀሰውን ጊዜ ሳይጠብቅ የፓርቲው ሙሉ አባል ሊሆን ይችላል፡፡
7.4 ተባባሪ አባል
- ዕድሜው ከ18 ዓመትና ከዚያ በላይ የሆነ፣ ከአዕምሮ ህመም ነፃ የሆነና በፖለቲካ ለመሳተፍ በሕግ ገደብ ያልተጣለበት፣ ነገር ግን በሙሉ አባልነት ለመስራትና ለመንቀሳቀስ የጤና ችግር፣ የጊዜ እጥረትና የቦታ አለመመቻቸት ያጋጠመው ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ተባባሪ አባል ሊሆን ይችላል፡፡
- ተባባሪ አባላት ለፓርቲ ኃላፊነት ቦታ ለመምረጥና ለመመረጥ፣ እንዲሁም በፓርቲው ውሳኔዎች ላይ ድምጽ ለመስጠት ካለመቻል በስተቀር ሌሎች የአባልነት መብቶች ሁሉ ይኖሯቸዋል፡፡
አንቀጽ 2.የአባልነት መዋጮ
ፓርቲው በመደበኛነት አባላት በሚያዋጡት መዋጮም የሚተዳደር ሲሆን፤አባላት እንደፍላጎታቸው በወርሃዊነት ወይም በዓመት ክፍያቸውን የመፈጸም ኃላፊነት አለባቸው፡፡የፖርቲው የአባላት ወርሃዊ መዋጮ መነሻ ክፍያ 50 ብር ሲሆን ይህን መክፈል የማይችል የድርጅቱ አባል ክፍያው በተደራጀበት መሠረታዊ ድርጅት ይታይለታል፡፡ ከመደበኛነት ውጭ ለፓርቲው የእለት ተእለት ስራ ለማንቀሳቀስ ግዜያዊ የመዋጮ ስርዓት የሚኖር ሲሆን፣ ይህም በፍጹም የአባላትን ፈቃደኝነትን መሰረት ያደረገ ብቻ ይሆናል፡፡
አንቀጽ 3፡- የአባልነት መብትና ግዴታ
9.1 መብት፡-
የፓርቲው አባል በስብሳባዎች ሃሳብ የማቅረብና የመሳተፍ፤በድርጅት መዋቅር ከታችኛው እስከላይ መዋቅሮች ሃሳብን የመግለጽና የመደመጥ መብት አለው
ማንኛውም የፓርቲው ሙሉ አባል የመምረጥና የመመረጥ እና ድምጽ የመስጠት መብት አለው
የፓርቲው አባል መታወቂያ ደብተር የማግኘት መብት አለው
የፓርቲው አባል መተዳደሪያ ደንብና ፕሮግራም መከበሩን የመከታተል መብት አለው
ማንኛውም የፓርቲው አባል የፓርቲውን ህልውና በማያናጋ እና አደጋ ላይ እስካልጣለ ድረስ ያለማንም ጣልቃገብነት ሃሳቡን በፈለገው መንገድ የመግለጽ መብት አለው
የፓርቲው አባል በራስ ተነሳሽነት አዳዲስና ጠቃሚ ሃሳቦችን የማፍለቅ፣ ለፓርቲ አመራር የማስተላለፍ፣ በፓርቲ እንቅስቃሴዎችና ተግባሮች የመሳተፍ መብት አለው
የፓርቲው አባል ድርጅታዊ መዋቅርን ጠብቆ ስለፓርቲው መረጃ የማግኘትና ሂስ የማቅረብ መብት አለው፤
ማንኛውም አባል በራሱ ፍላጎት አባልነቱን የመተው መብት አለው፤ በሚለቅበት ጊዜ መልቀቁን ከእነምክንያቱ ወደ ፓርቲው ለመለመለው አካል በፅሑፍ ማስታወቅ ይኖርበታል፡፡
ማንኛውም አባል በፖርቲው የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የመሳተፍ መብት አለው፡፡
9.2. ግዴታ
የፓርቲውን ዓላማና ፕሮግራም ተግባራዊ ማድረግ፣ ለህዝብ ማስተዋወቅና ማሰራጨት
የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብና መመሪያዎች ማክበርና የፓርቲውን አመራር ውሳኔዎች ተግባራዊ ማድረግ
በተለያዩ ቋሚና ጊዜያዊ ኮሚቴዎችና፣ ፓርቲው በሚጠራቸው የተለዩ ስብሰባዎች መሳተፍ
የአባልነት መዋጮን በወቅቱ መክፈልና በፓርቲ የገንዘብ መዋጮ ተግባራት መሳተፍ
ለፓርቲው ታማኝ መሆንና ሚስጥር መጠበቅ
በብሄረሰብ ልዩነትና በቀለም፣ በቋንቋና በመሳሰሉት ምክንያቶች መለያየትና መከፋፈልን ከመፍጠር በአሉባልታ ላይ ተመሥርቶ ሌሎች የፓርቲ አባላትን ከማሳደም ራስንና ሌሎችን ማራቅ፡፡
የፓርቲውን ኘሮግራምና ዓላማ፣ አንድነትና ሕብረት ከሚጐዱ ማናቸውም እንቅስቃ ሴዎችና የሥነ-ምግባር ጉድለቶች መቆጠብ
ከአንጀነት፣ ከአሉባልተኝነትና ከከፋፋይነት መቆጠብ
9.ለመልካም ዜግነት ራስን ከግድፈቶች ሁሉ መቆጠብ
ለስነምግባር መርሆችና ለህግ ተገዢ መሆን
ሌሎች የፓርቲውን ዓላማና ኘሮግራም የሚያራመዱ ግዴታዎችን መወጣት፡፡
አንቀጽ 4፡- አባልነት የሚቋረጥባቸው ሁኔታዎች
የፓርቲው አባል በራሱ ፍላጎት አባልነቱ እንዲቋረጥ በፅሁፍ ጥያቄ ሲያቀርብ
የፓርቲው አባል በሞት ሲለይ
የፖርቲው አባል በህግ ችሎታ ሲያጣ
የፓርቲው አባል በሥነ-ስርዓት ጉዳዮች ላይ ለመወሰን በፓርቲው ውስጥ ሥልጣን ባለው አካል ከአባልነት እንዲባረር ሲወሰን
የፓርቲው አባል ጊዜው ማለፉን እያወቀ ለሶስት ተከታታይ ወራት ያለበቂ ምክንያት የአባልነት መዋጮ ሳይከፍል ሲቀር፡፡